ባለፈው ሳምንት በናይሮቢ የተፈፀመውን ጥቃት ተከትሎ የተጠረጠሩ አራት ግለሰቦች በማረሚያ ቤት እንዲቆዩ ፍርድ ቤት ወሰነ



ወደ መተላለፊያው ከመሄዳቸው በፊት ቦምቦችን ወርውረው አፈንድተዋል/ ሮይተርስ

ፍርድ ቤቱ በማረሚያ ቤት የሚቆዩት 10 እስከ 30 ቀናት ነው ሲል ውሳኔ አሳልፏል፡፡


በምስራቅ አፍሪካ ተደጋጋሚ የሽብር ጥቃት እየፈፀመ ያለው የአልቃይዳው ክንፍ አልሸባብ ከሶማሊያ ቀጥሎ ኬንያን የሽብር ክንዱን አዘውትሮ የሚያሳርፍባት ሃገር አድርጓታል፡፡

አሸባሪ ቡድኑ በሃገሪቱ በተደጋጋሚ በሚፈፅመው የቦምብ ጥቃት በርካቶቹን ለህልፈት እና ለአካል ጉዳት ዳርጓቸዋል፡፡
እንደ አልጀዚራ ዘገባ ፅንፈኛው ቡድን ባለፉት አምስት አመታት ውስጥ በኬንያ ብቻ 20 ጊዜ በላይ ጥቃት ፈፅሞ 300 ሰዎችን ገድሏል፡፡

ባለፈው ሳምንት ቡድኑ ናይሮቢ በሚገኝ ግዙፍ ህንፃ ላይ ባደረሰው ጥቃት 21 ኬንያውያን ሲገደሉ ከታጣቂው ቡድን በኩል ደግሞ 5 ሰዎች ተገድለዋል፡፡

ዶናልድ ትራምፕ ኢየሩሳሌን የእስራኤል መዲና በማለት እውቅና መስጠታቸውን ተከትሎ ጥቃቱን እንደፈፀመው የገለፀው አል ሸባብ ጥቃት እንዲፈፅሙ ከላካቸው ታጣቂዎች መካከል ሶስቱ ኬንያውያን መሆናቸውን በደህንነት ካሜራ በኩል ታውቋል ብሏል አልጀዚራ በዘገባው፡፡

የናይሮቢ ፍርድ ቤት 20 ሰዓት የቆየውን ጥቃት ተከትሎ አራት የተጠረጠሩ ግለሰቦች በማረሚያ ቤት እንዲቆዩ ወስኗል፡፡
ፍርድ ቤቱ በማረሚያ ቤት የሚቆዩት 10 እስከ 30 ቀናት ነው ሲል ውሳኔ አሳልፏል፡፡
እንደ ፍርድቤቱ ውሳኔ ሶስቱ ተጠርጣሪዎች 30 ቀናት እንዲሁም አራተኛው ተጠርጣሪ 10 ቀናት በማረሚያ ቤት እንዲቆዩ ፍርድ ተሰጥቷቸዋል፡፡

የካናዳ ዜግነት ያለው ግለሰብን ጨምሮ ሌሎች ስድስት ተጠርጣሪዎችም ለምርመራ ማረሚያ ቤት እንዲቆዩ ብይን መስጠቱን ሲጂቲኤን ዘግቧል፡፡



Post a Comment

0 Comments